አልሚዎች በተገደበ የጊዜ ሰሌዳ ዘመኑን የዋጀ የግንባታ ጥበብ እና ቀልጣፋ አሰራርን በመከተል የተላለፉ ቦታዎችን አልምተው ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አቶ መኮንን ያኢ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ በካብኔ ውሳኔ በሞል፣ በሆቴልና አፖርትመንት ዘርፍ ለመሰማራት መሬት በምደባ ከወሰዱ አልሚዎች ጋር ምክክር አድርጓል፡፡
ከአርባ በላይ አልሚዎች በተሳተፉበት በዚህ መድረክ የተላለፉ መሬቶች በቅርቡ በሀገራችን ለሚካሄደው ኮፕ 32 ጉባኤ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ዝግጁ እንዲሆኑ ታስቦ ስለመዘጋጀቱ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ መኮንን ያኢ ተናግረዋል፡፡


ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ከተላለፉ ቦታዎች የተወሰኑ አልሚዎች በገቡት የሊዝ ውል መሠረት የሚጠበቅባቸውን ፎርማሊቲ አሟልተው ወደልማት መግባት ያልቻሉ መሆናቸውን አረጋግጠናል ያሉት የቢሮው ኃላፊ ከዚህ በኋላ ግን የተላለፉ ውስን የሆነውን የመንግስትና የህዝብ ኃብት አጥሮ መያዝ እንደማይቻል ገልፀዋል፡፡
አክለውም ቢሮው ለስራው መሳካት ተጠያቂነት ባለው መልኩ ከሌብነት ተግባራት የፀዳ የጠራ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ያለ ባለኃብቱ ተሳትፎ የአንድን ሀገር እድገት ማረጋገጥ እንደማይቻል እንገነዘባለን ያሉት ተሳታፊ ባለሀብቶች ከቢሮው ጋር በቅርበት በመስራት የተረከቡትን ቦታ በማልማት ለአገልግሎት ዝግጁ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡
ምንጭ: መሬት ልማት አስተዳደር


















